@habteman832: # የቅዱስ # ሩፋኤል # ታሪክ ቅዱስ ሩፋኤል ቊጥሩ ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት ሲኾን፤ ሩፋ ማለት ሐኪም፤ ኤል ማለት እግዚአብሔር ማለት ሲኾን ሩፋኤል ማለት “እግዚአብሔር ሐኪሜ ነው” ማለት ነው፤ ሄኖክም “በሰው ቁስል ላይ የተሾመ ከከበሩ መላእክት አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ነው” ይለዋል (መጽሐፈ ሄኖክ 6፥3):: ይኽ መልአክ በራማ ሰማይ ያሉ ነገደ መናብርትን የሚመራቸው ነው፡፡ ነገደ መናብርት ያላቸው ቅዱስ ሩፋኤል የሚመራቸው በራማ ሰማይ የሚኖሩ ነገደ መላእክት ናቸው፡፡ ቅዱስ ኤጲፋንዮስም በሥነ ፍጥረት መጽሐፉ ላይ “ወለዳግም ጾታ ዐሠርቱ ስሞሙ መናብርት ወሊቆሙ ሩፋኤል እሉ እሙንቱ እለ ይቀልል ሩጸቶሙ እምነፋስ ወእለ ይጸውሩ ወላትወ መብረቅ ወኲናተ እሳት ዘይነድድ ወአንበሮሙ በዳግሚት ሰማይ” ይላል በራማ ሰማይ የሚገኘውን ኹለተኛውን ዐሥሩን ነገድ መናብርት ሲላቸው አለቃቸው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፤ እነዚኽም ረቂቅ የኾነ የመብረቅ ጋሻ የእሳት ጦር ይዘው ከነፋስ ይልቅ የፈጠኑ ሲኾኑ በራማ በኹለተኛው ክፍል ላይ አስፍሯቸዋል፡፡ ቅዱስ ሩፋኤል ከሚመራው ከዚኽ ነገድ 24ቱ ካህናተ ሰማይ ወጥተዋል፡፡ አባ ጊዮርጊስም በሰዓታቱ ላይ፡- “ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር ጽርሐ አርያም ማኅፈዱ መካነ ትጉሃን ዐጸዱ ካህናተ ሰማይ ቅዉማን በዐውዱ አክሊላቲሆሙ ያወርዱ ቅድመ መንበሩ እንዘ ይሰግዱ ይርዕዱ ወኢይዝብጦሙ ሶበ ይበርቅ ነዱ” (ጽርሐ አርያም አዳራሹ፤ የትጉሃን መኖሪያ ቦታው የሚኾን እግዚአብሔር ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ ተብሎ በአንድነት በሦስትነት ይመሰገናል፤ ካህናተ ሰማይ በዙሪያው ይቆማሉ፤ በዙፋኑ ፊት እየሰገዱ አክሊሎቻቸውን ያወርዳሉ፤ እሳትነቱ (ባሕርዩ) በሚበርቅ፣ ወገግ በሚል ጊዜ እንዳይመታቸው ይንቀጠቀጣሉ) ይላል ሊቁ እንደጠቀሰው በዕለተ እሑድ ሥሉስ ቅዱስ ሰባቱን ሰማያት ፈጥረዋል፤ ከዚያም ልዑል እግዚአብሔር በዕለተ እሑድ ሰባቱን ሰማያት ከፈጠረ በኋላ ሊቁ በአክሲማሮስ እንደገለጸው ከቅዱሳን መላእክት መኻከል፡- “ወእምዝ ነሥአ እግዚአብሔር እምሰራዊተ ሩፋኤል ፳ወ፬ተ ሊቃናተ ወአቀሞሙ ዐውደ መንበሩ፤ ወሰመዮሙ ለእሙንቱ ካህናተ ሰማይ ወወሀቦሙ ማዕጠንታተ ዘእምወርቀ እሳት ወአክሊላተ ብርሃን ዘእምጳዝዮን ወአብትረ ዘከተማሆን መስቀል ወአልበሶሙ አልባሰ ክህነት” ይላል ከሰራዊተ ሩፋኤል ፳፬ት ሊቃናትን መርጦ በመንበረ ስብሐት በመጋረጃዋ ውስጥ ዙሪያዋን ክንፍ ለክንፍ ገጥሞ አቁሟቸዋል (ሕዝ ፩፥፲፩-፲፪)፤ ቊጥራቸውን ኻያ አራት ማድረጉ በኻያ አራቱ ጊዜያት ጸልየው ሌላውንም ራሳቸውንም ጠብቀው ዋጋቸውን ተቀብለው የሚኖሩ በመኾናቸው ሲኾን እነዚኽንም መላእክት “ካህናተ ሰማይ” ሲላቸው የእሳት የወርቅ ጽና ሲያሲዛቸው የብርሃን አክሊል ጳዝዮን የሚባል የብርሃን ዘውድ ደፍቶላቸዋል፤ የብርሃን ዘንግ ማኅተሙ መስቀል የኾነ ሲያሲዛቸው የብርሃን ካባ ላንቃ ሕብሩ መብረቅ የመሰለ አልብሷቸዋል ( ራእ ፬፥፬-፭፤፲-፲፩)። እነዚኽ ሰማያውያን ካህናት በአንድ ላይ ባጠኑ ጊዜ ዛሬ በክረምት ጊዜ ጉም ተራራውን እንደሚሸፍነው ከማዕጠንታቸው የሚወጣው ጢስ መልኩ መብረቅ፣ ድምፁ ነጐድጓድ፣ መዐዛው መልካም የኾነና ጽርሐ አርያም፣ መንበረ መንግሥት የተባሉትን የብርሃን ሰማያት የሚሸፍንና የሚጋርድና ከጢሱ ጋር የቅዱሳን ጸሎት ዐብሮ ወደ እግዚአብሔር ፊት ይወጣል፤ “ሌላም መልአክ መጣና የወርቅ ጥና ይዞ በመሠዊያው አጠገብ ቆመ፤ በዙፋኑም ፊት ባለው በወርቅ መሠዊያ ላይ ለቅዱሳን ኹሉ ጸሎት እንዲጨምረው ብዙ ዕጣን ተሰጠው የዕጣኑም ጢስ ከቅዱሳን ጸሎት ጋር ከመልአኩ እጅ በእግዚአብሔር ፊት ወጣ” እንዳለ ዮሐንስ በራእዩ (ራእ ፰፥፫-፭)፡፡ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ በአክሲማሮስ ላይ “ወቦ ኪሩቤል ይቀውሙ በየማን በአምሳለ ቀሳውስት ወሱራፌል ይቀውሙ በአምሳለ ዲያቆናት ወድኅሬሆሙ ካህናተ ሰማይ ወቦ እልፍ አእላፋት ወትእልፊተ አእላፋት መብረቅ ወነጐድጓድ ወሠረገላሆሙኒ ምሉኣነ አዕይንት” እንዳለ ኪሩቤል በቀኝ ሱራፌል በግራ ከፍ ብለው ካህናተ ሰማይ ክንፍ ለክንፍ ገጥመው በስተኋላቸው ሲታዩ በሰማይ ውዱድ ዙሪያ እልፍ አእላፋት መብረቅ፣ ነጐድጓድ፣ ሠረገላ፣ እንደ መስታየት ብሩህ የኾነ ሲኖርበት እነዚኽ ቅዱሳን መላእክትም ሳያቋርጡ “ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ እግዚአብሔር” እያሉ ፈጣሪያቸውን በአንድነቱ በሦስትነቱ ያመሰግኑታል (ራእ ፬፥፰)፡፡ ሊቁ ቅዱስ ባስልዮስም ስለነዚኽ ቅዱሳን መላእክት ሲገልጽ “ወኲሎሙ ሰራዊተ መላእክት እለ ይቀውሙ ቅድሜሁ ይጸርሑ ወይባርክዎ ለእግዚአብሔር…” (በፊቱ የሚቆሙ የመላእክት ሰራዊትም ኹሉ ጩኸው ያመሰግኑታል፤ የመላእክት አለቆችም ለማይታይ ለባለዚኽ ስም ዘንበል ብለው ይሰግዳሉ፤ እግዚአብሔርን የሚያመሰግኑና የሚዘምሩ ዙፋኑን የሚሸከሙ አርባዕቱ እንስሳ ጩኸው ያመሰግኑታል፤ ዕጣንን የተመሉ የወርቅ ማዕጠንት በእጆቻቸው ያለ ኻያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ይኸውም የቅዱሳን ጸሎት ነው እስከ ዘላለሙ ሕያው በኾነው ፊት የሚቀበለው መሥዋዕት አድርገው ወደ ላይ ያሳርጋሉ) በማለት የቅዱሳንን ጸሎት ቅድመ እግዚአብሔር በማዕጠንታቸው ለማሳረግ የተመረጡት መላእክት ኻያ አራቱ ካህናተ ሰማይ መኾናቸውን አስተምሯል፡፡ ይኽ መልአክ ጦቢትን የተራዳ መልአክ ነው፤ ይኽ ጦቢት ዐሥሩ ነገድ በ፯፻፳ ቅድመ ልደተ ክርስቶስ ሲማረኩ ዐብሮ የተማረከ ጻድቅ ሰው ነው፤ ይኽ ሰውን በመርዳት በደግነቱ የታወቀው ጦቢት ከመንገድ ወድቆ የተገኘ በድን ቀብሮ፤ በዚያው ሌሊት ከቅጥሩ አጠገብ ፊቱን ተገልጦ ተኝቶ ሳለ አዕዋፍ ትኩስ ፋንድያ ዐይኑ ላይ ጥለውበት እንደ ብልዝ ያለ ወጥቶበት ዐይኑ ጠፋ፤ ሚስቱም ባለማስተዋል “አይቴ ውእቱ ምጽዋትከ ወጽድቅከ” (በጐነትኽ ምጽዋትኽ ያዳነኽ ወዴት ነው?) በማለት በተናገረችው ጊዜ ዐዝኖ ሞትን ተመኘ (ጦቢ ፪፥፲፬)፡፡ ያን ጊዜ መልአኩ ሩፋኤል ርሱንና ባሎቿ ስለሞቱባት ቤተሰቦቿ ያንቋሽሿት የነበረችውን የራጉኤል ልጅ ሳራን ለማዳን ተልኮ በመምጣት አስቀድሞ በርሷ ላይ ዐድሮ ባሎቿን ይገድልባት የነበረውን ጋኔን አስወጥቶ የጦቢት ልጅ ጦብያ እንዲያገባት አድርጓል፤ በዚኽም “ፈታሔ ማሕፀን” ተብሏል፡፡ በኋላም ወደ ጦቢት በመኼድ ረዥም ዘመን የታወረ ዐይኑን አብርቶለት “አነ ውእቱ ሩፋኤል መልአክ አሐዱ እምነ ሰብዐቱ ቅዱሳን መላእክት” (ከሰብዐቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ሩፋኤል እኔ ነኝ) ብሏቸው ተሰውሯል (ጦቢ ፲፪፥፲፭)፡፡ የቅዱስ ሩፋኤል በረከት ይደርብን ወስብሓት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክብር አሜን
Habte Man832
Region: ET
Sunday 07 September 2025 14:43:16 GMT
Music
Download
Comments
etsub :
❤❤❤❤
2025-09-07 17:06:41
1
meazi :
🙏🙏🙏
2025-09-07 16:54:13
1
ንጋት የማርያም ልጅ 2123 :
🥰🥰🥰
2025-09-08 19:07:40
0
የማሪያም ልጅ :
🥰🥰🥰
2025-09-10 20:26:05
0
zerhjuen tes :
🥰🥰🥰
2025-09-30 07:41:31
0
sammy Alex :
🤩🤩🤩
2025-09-07 18:44:15
0
wede love :
🥰🥰🥰
2026-05-12 22:08:33
0
To see more videos from user @habteman832, please go to the Tikwm
homepage.